#ኮይሻ #ጨበራጩርጩራ #ኦሞ #ደቡብምዕራብ#ቦንጋ የደቡብ ምዕራብ ኢትየጵያ ድንቅ የተፈጥሮ ስጦታዎች

1 year ago
582

ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል አምስቱ ዞኖች እና አንድ ልዩ ወረዳ ያለው ሲሆን እነዚህም የኮንታ ልዩ ወረዳ፣ የምዕራብ ኦሞ ዞን፣ የቤንች ሸኮ ዞን፣ የካፋ ዞን፣ የዳውሮ ዞን እና የሸካ ዞን ናቸው።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል 39ሺህ 64ኪሎ ሜትር2 የቆዳ ስፋት እንዳለው የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ሕዝበ ውሳኔ ማስፈፀሚያ ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት መረጃ ያሳያል።
የክልሉ ሕዝብ በዋናነት በጥምር ግብርና የሚተዳደሩ ሲሆን በአርብቶ አደርነት የሚተዳደሩም እንዳሉ ይገለጻል።
ክልሉ በምሥራቅ የደቡብ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል፣ በሰሜን የኦሮሚያ ክልል፣ በምዕራብ የጋምቤላ እንዲሁም ደቡብ ሱዳን ያዋስኑታል።
በክልሉ እንደ ጨበራ ጩር ጩራ እና ኦሞ ብሔራዊ ፓርክ ያሉ የተለያዩ የቱሪስት መስህቦች ይገኛሉ።
በዳውሮ ዞን እና ኮንታ ልዩ ወረዳ መካከል የሚገኘው እና ከ29 የሚበልጥ አጥቢ የዱር እንስሳትን በውስጡ የያዘዉ የጨበራ ጩርጩራ ብሔራዊ ፓርክ የአገር ጎብኚዎች መዳረሻ በመሆን እያገለገለ ይገኛል።
በፓርኩ ዝርያው እየተመናመነ የመጣዉ የአፍሪካ የዝሆን፣ ጎሽ፣ ዲፋርሳ፣ ከርከሮ፣ ሳላ እና እንደ አጋዘን ያሉ የዱር እንስሳት ይገኛሉ።
በዚሁ ክልል ከሚገኙ የተፈጥሮ መስህቦች መካከል አንዱ የንጉሥ ሃላላ የድንጋይ ካብ አንዱ ሲሆን መገኛውም ዳውሮ ዞን ነው።
የሃላላ ካብ ከ175 ኪ.ሜትር በላይ ርዝመት ያለውና አሰራሩ አስገራሚ የሆነዉ የድንጋይ ካብ የዚሁ ክልል የቱሪስት መስህብ ነው።
በገበታ ለአገር ከሚለሙ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ የሆነው ኮይሻ ፕሮጀክት የሚገኘው የዚሁ አዲስ ክልል አካል በሆነው በኮንታ ልዩ ወረዳ ነው።
በተጨማሪም በሸካ ዞን የሚገኘው ጥብቅ ደን፣ የከፋ የጫካ ቡና እንዲሁም ሰፊ ሽፋን ያለው ደን የዚሁ ክልል አካላት ናቸው።
የኦሞ ብሔራዊ ፓርክ በዚሁ ክልል የሚገኝ ሲሆን በውስጡም ልዩ ልዩ የዱር እንሰሳትና ዕፅዋት ይገኙበታል።
75 አጥቢ እንስሳትንና 325 የአዕዋፍ ዓይነቶችን እንደያዘ የሚነገረው ይህ ብሔራዊ ፓርክ፣ ውድንቢዎች፣ የመጋላ ቆርኪ መንጋ፣ ሳላዎች፣ የሜዳ ፍየሎች እና ሌሎም አጥቢዎች ይገኛሉ።
ውድንቢ በኢትዮጵያ በኦሞ ብሔራዊ ፓርክ ብቻ የሚገኝ የዱር እንሰሳ ነው።
በክልሉ በሰፊው እንደሚገኝ የሚነገረው የብረት እና የድንጋይ ከስል ማዕድናትን ተከትሎ በዳውሮ እና ኮንታ አካባቢዎች ፋብሪካዎች እየተገነቡ ይገኛሉ።
በክልሉ በ2014 ዓ.ም 3̂.6 ሚሊዮን ሕዝብ ገደማ ይኖርበታል ተብሎ ይገመታል።
በክልሉ 13 ነባር ብሔረሰቦች ያሉ ሲሆን ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በመምጣት ተቀላቅለው የሚኖሩ ሕዝቦችም ይገኙበታል።
በዚህ የክልሉ ረቂቅ ሕገ መንግሥት ላይ የክልሉ የሥራ ቋንቋ አማርኛ ይሆናል ተብሎ የተቀመጠ ሲሆን፣ በየእርከኑ ያሉ አካላት ደግሞ የየራሳቸውን የሥራ ቋንቋ እንዲወስኑ ይደነግጋል።
በክልሉ ከ1.3 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ በመያዝ የከፋ ዞን ቀዳሚ ሲሆን፣ በዞኑም ከፊኛ ይነገራል።
በክልሉ በሕዝብ ብዛት ሁለተኛ የሆነው የዳውሮ ዞን ሲሆን ዳውሮኛ ደግሞ ቋንቋው ነው።
በቤንች ሸኮ አራት የሚሆኑ ብሔረሰቦች የሚገኙ ሲሆን ሁሉም የየራሳቸው ቋንቋ አላቸው።
ሸካም እንደዚሁ ሦስት፣ ምዕራብ ኦሞም አራት ብሔረሰቦች ይኖሩበታል።
በተጨማሪም ኮንታ ልዩ ወረዳ የራሱ የሆነ ቋንቋ አለው።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል አዲስ የከተሞች ማዕከላትን ለመስተዳደሩ ተቋማት ለማደራጀት ወስኗል።
ሌሎቹ ክልሎች ማዕከላቸውን በአንድ ዋና ከተማ አድርገው ቢሮዎቻቸው በአንድ ስፍራ ላይ እንዲዋቀሩ በማድረግ ይታወቃሉ።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ግን ከሌሎቹ በተለየ ለየት ያለ አደረጃጀትን ለመከተል መርጧል።
ሐምሌ 27/2014 ዓ.ም. የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል አራት ዋና ከተሞች እንዲኖሩት የሚያስችል ረቂቅ አዋጅ ለክልሉ ምክር ቤት አቅርቧል።
በረቂቁ መሰረት ክልሉ ካሉ ስድስት ዞኖች በአራቱ የዞን ከተሞች የክልሉ መስተዳደር ዋና ዋና አካላት መቀመጫ ይሆናሉ።
በረቂቁ መሠረትም ቦንጋ የፖለቲካ እና የክልሉ ርዕሰ መስተዳደሩ ጽህፈት ቤት መቀመጫ ትሆናለች።
ተርጫ የክልሉን ምክር ቤት መቀመጫ፣ ሚዛን አማን የዳኝነት መዋቅሩ የሚገኝበት እንዲሁም ቴፒ የብሔረሰቦች ምክር ቤት መቀመጫን ይይዛሉ።
ሥራ አስፈጻሚ ቢሮዎች ደግሞ በአራቱም ከተሞች ፍትሃዊ ሆነው ይመደባሉ ተብሏል።
ይህ አዲስ የክልል አደረጃጀት የክልሎችን ሥራና ሃብት በአንድ ከተማ ላይ ብቻ በማከማቸትና በማፍሰስ ከሌሎች ከተሞች በበለጠ አንድ ከተማ ብቻ በላቀ ሁኔታ እንዲያድግና ተጠቃሚ እንዲሆን የሚያደርገውን አሰራር ይለውጣል በሚል እሳቤ የታቀደ ነው።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል የተመሠረተው መስከረም 20 ቀን 2014 ዓ.ም. በተደረገው ሕዝበ ውሳኔ በክልልነት የመደራጀቱ ሐሳብ ከ98 በመቶ በላይ የሆኑ መራጮችን ድምፅ በማግኘት ሲሆን፣ በአንድ ላይ የተሰበሰቡ የካፋ፣ የሸካ፣ የቤንች ሸኮ፣ የዳውሮና የምዕራብ ኦሞ ዞኖች፣ እንዲሁም የኮንታ ልዩ ወረዳ በኅዳር ወር በይፋ ክልል መሥርተዋል፡፡
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ሲደራጅ ያለው የሕዝብ ብዛት፣ ከደቡብ ክልል አጠቃላይ ሕዝብ ብዛት 19.4 በመቶውን የሚይዝ በመሆኑ፣ ከክልሉ ሀብትና ዕዳ ይህንኑ መጠን እንዲካፈል ተወስኗል፡፡ በዚህም ደቡብ ምዕራብ እስከ ኅዳር 30 ቀን 2014 ዓ.ም. ከደቡብ ክልል ጋር አብሮ ሲያወጣው ከነበረው ወጪ ቀሪ የሆነ ሀብት 19.4 በመቶ፣ የፌዴራል ድጎማ በጀትና 122 ተሽከርካሪዎችን ተካፍሏል፡፡
የክልል ዋነኛ የኢኮኖሚ መሠረት ግብርና ሲሆን፤ዋና ዋና ምርቶችም በቆሎ፣ ስንዴ፣ ጤፍ፣ ጥራጥሬ፣ ድንች፣ እንሰት፣ ፍራፍሬዎችና የቅባት ሰብሎች ናቸው።ዋነኛው ምርት በእህል ራስን ለመቻል የሚያስችሉ ሲሆኑ ጐን ለጐን ገበያ ተኮር የሆኑ ቡና፣ ሻይ ቅጠል፣ ጐማ ተክል ወዘተ እንዲሁም ማንጐ፣ አኘል፣ አቦካዶ፣ አናናስ፣ ፓፓያና ሙዝ በስፋት ይመረታል። የቁም ከብቶች ወተትና የወተት ተዋፅኦም ይገኛል።

ከግብርና በተጨማሪም በንግድና ኢንዱስትሪ ዘርፍ በግንባታ፣ እንጨትና ብረታ ብረት፣ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት የተደራጁ ማኀበራት ይገኛሉ።
ATTRIBUTIONS
SOURCE: Ethiopian instrumental Music | ከወፎች ዝማሬና ከፏፏቴ ድምፅ ጋር | Ethiopian Classical Music| Ethiopian Music - YouTube
CREATED BY: Yichalal ይቻላል - YouTube
SOURCES:
https://www.bbc.com/amharic/articles/cxe5p05ylvlo
https://www.ethiopianreporter.com/78973/
https://am.wikipedia.org/wiki/%E1%8B%B0%E1%89%A1%E1%89%A5_%E1%89%A5%E1%88%94%E1%88%AE%E1%89%BD_%E1%89%A5%E1%88%94%E1%88%A8%E1%88%B0%E1%89%A6%E1%89%BD%E1%8A%93_%E1%88%95%E1%8B%9D%E1%89%A6%E1%89%BD_%E1%8A%AD%E1%88%8D%E1%88%8D

Loading comments...