በትረ ሙሴ (አርዌ ብትር) ምንድነው? | ከ 666 ከዘንዶው ጋር ምን አገናኘው? | ይመለክበታል?

2 years ago

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቅዱስ ፓትሪያርኩን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳቱ ሁሉ በእጃቸው በሚይዙት በትር ላይ የለው እባብ ምንድነው ? ብለው ለሚጠይቁ ሁሉ የተሰጠ ምላሽ 👇

ጥያቄው የቆየ እና በተለይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ የአደባባይ በዓላት በሚደረጉ ጊዜ በተደጋጋሚ የሚነሣ ነው ፣ አንዳንዶችም ከዘንዶ እና 666 አምልኮ ጋር በማያያዝ ምስጢሩን ባለመረዳት በድፍረት ይናገራሉ ፣

"ይቅር ይበላቸው" እያልን ይኽ ምስሉ ላይ በበትሩ ግራ ቀኝ ተጠምጥሞ የምትመለከቱት በመጀመሪያ የእንባብ እምጂ የዘንዶ አይደለም።
የበትሩ ስምም በትረ ሙሴ (አርዌ ብትር) ይባላል።

አርዌ ማለት በግእዝ አውሬ ማለት ሲሆን ለምሣሌ :- አውራሪስ (አርዌ ሀሪስ -ባለ አንድ ቀንድ አውሬ እንደማለት ነው) አዊት እንስሳትን የሚገልጽ ጥቅል ስም ነው "አርዌ"
የአውሬ እባብ በትር የሚል ትርጓሜ አለው በሌላ ስሙ በትረ ሙሴ ይኽም እንዴት እንደሆነ እናያለን 👇

እባቡም እንደምትመለከቱት ከመስቀሉ ስር ነው የሚታየው ። ምክንያቱም መስቀል የሁሉም የበላይና "እባብ" የተሰኘው ዲያብሎስም አናት አናቱን የተቀጠቀጠበት ነውና ።

ማቴ 22÷29
"ኢየሱስም፡መልሶ፡እንዲህ፡አላቸው፦ [መጻሕፍትንና፡የእግዚአብሔርን፡ኀይል፡አታውቁምና፡ትስታላችኹ]

👉 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አብያተ ክርስቲያናትን የሚመሩ ቅዱሳን ፓትርያርኮችና ሊቃነ ጳጳሳት ፣ ኤጲስ ቆጶሳትም በእጃቸው የሚይዙት አርዌ ብርት/መስቀልና የእባብ ምልክት ያሉበት/ በትር ምሳሌነቱ

✔ ከመስቀሉ ስር ያለው እባብ ሙሴ ለሕዝቡ መዳኛ ያደረገው የናስ እባብ ምሳሌ ነው።

“ሙሴም የናሱን እባብ ሠርቶ በዓላማ ላይ ሰቀለ እባብም የነደፈችው ሰው ሁሉ የናሱን እባብ ባየ ጊዜ ዳነ” ። ዘኍ 2፣ 19

ይኼ ምሳሌ መሆኑን ክርስቶስ በዮሐ 3÷14 ላይ ሲያስተምር እንዲኽ ብሏል 👇

“ሙሴም በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል ይገባዋል”

በማለት ምሳሌና ጥላ የነበረውን አማናዊ ለማድረግ፣ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰቅሎ ያዩት ሁሉ እንደሚድኑ አመሳስሎ አስተማረበት።

ኢየሱስ ክርስቶስ የናሱን እባብ ከራሱ ስቅለት ጋራ ሲያነጻጽረው ያላፈረበትን፤ የእኛ አባቶች የናሱን እባብ ምሳሌ “በትረ ሙሴ” የሚባለውን በግራ እጃቸው፣የተሰቀለበትን መስቀል በቀኝ እጃቸው ቢይዙ የሚያሳፍር አይሆንም፡፡

በብሉይ እግዚአብሔር ሕዝቡ ሲበድሉት “እባቦችን ሰደደ፥ሕዝቡንም ነደፉ ከእስራኤልም ብዙ ሰዎች ሞቱ”
ዘኍ 21፡6

በእባብ መርዝ ተነድፈው የታመሙ ሁሉ ፣ መርዝ የሌለው የናስ እባብ በማየት እንዲድኑ አድርጓል።

ይህም ምሳሌው ለእኛ ነው፡፡

የበደሉት እስራኤላውያን የእኛ የሰዎች ምሳሌ ሲሆኑ ፤ መርዝ ያለው እባብ የዲያብሎስ ምሳሌ ነው ፤ የናስ እባብ መርዝ እንደሌለው ሁሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ያለ በደሉ ተሰቅሎ ስለ እኛ ኃጢአት እርሱ የመሞቱ ምሳሌ ነው።

“እባብን ሠርተህ በዓላማ ላይ ስቀል የተነደፈውም ሁሉ ሲያያት በሕይወት ይኖራል” ዘኍ 21፣8 መባሉ፣  የናሱን እባብ ሲያዩ የዳኑ፣ ጌታ ተሰቅሎ አይተው የዳኑ ሰዎች ምሳሌ ሲሆን፣

ከሩቅ ያሉት ሰዎች ምሳሌነት ወንጌልን ከመምህራን በመስማት ሳያዩ ቃሉን ብቻ ሰምተውና አምነው የዳኑ ክርስቲያኖች ምሳሌ ነው፡፡
ምክንያቱም በስብከታቸው “በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር ገላ 3፣1 እንዳሉት ማለት ነው፡

ፓትርያሪኮች ለምን ይይዙታል⁉

የናሱ እባብ የክርስቶስ ምሳሌ እንደሆነ ሁሉ ፣ በትርም የፈጣሪያችን የእየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ እና ጥላ ነው። ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፣ ከስሩም ቁጥቋጦ ያፈራል። ኢሳ 11:1 ስላለ የእሴይ እና የዳዊት ልጅ የሆነው የጌታችን እየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ የመያዛቸው ምልክት ነው።

በኃላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር እራሱን ይካድ መስቀሉንም ዕለት ዕለት ተሸክሞ ይከተለኝ ሉቃስ 9:23 ብሏልና በየግዜው መስቀለ ክርስቶስን በእጃቸው ይዘው በሕይወታቸው ደም መከራ መስቀልን ታግሰው እረኝነታቸውን የሚያሳዩበት ተግባራዊ ምልክት ነው።

ሙሴ በትር ይይዝና ተአምራት ያደርግ ነበረ፤ “ይህችንም ተአምራት የምታደርግባትን በትር በእጅህ ይዘሃት ሂድ” ዘጸ 4፣17 ያለው እግዚአብሔር ያለ በትር ተአምር ማድረግ ተስኖት ሳይሆን አንተ መሪያቸውና ቤዛ ሆነህ የምታወጣቸው ነህ ሲለው ነው በትሩን አስይዞ የላከው።

ለዚህ ነው “ሹምና፡ፈራጅ፡እንድትኾን፡የሾመኽ፡ማን፡ነው? ፣ ብለው፡የካዱትን፥ይህን፡ሙሴን፡በቍጥቋጦው፡ በታየው፡በመልአኩ፡እጅ፡እግዚአብሔር፡ሹምና፡ቤዛ፡አድርጎ፡ላከው።" ሐዋ 7፣35 ብሎ የመሰከረለት፡፡

የዕብራውያን ሁሉ አባት ያዕቆብ ዘንግ ይይዝ እንደነበርና ፣

"ያዕቆብ፡ሲሞት፡በእምነት፡የዮሴፍን፡ልጆች፡እያንዳንዳቸው፡ባረካቸው፥በዘንጉም፡ጫፍ፡ተጠግቶ፡ሰገደ። ዕብ 11:21 ተብሎ የተጻፈው አባቱ ዘንግ ስለሚይዝ ነው።

በተጨማሪም እረኛው ዳዊት * በትር ይዞ* 1ኛ ሳሙኤል 17:43 በጎቹን እንደሚጠብቅ ከፍልሥጤማውያን ጋር ውጊያ ሊያደርግ ባለም ጊዜ ይዞት እንደነበር

"ፍልስጥኤማዊውም፡ዳዊትን፦በትር፡ይዘኽ፡የምትመጣብኝ፡እኔ፡ውሻ፡ነኝን፧አለው።"

በኃላም የህዝብ ጠባቂ ንጉስ ሲሆን በትረ መንግስት እንደሚይይዝ ዘፍ 49:10

"በትረ፡መንግሥት፡ከይሁዳ፡አይጠፋም፥የገዢም፡ዘንግ፡ከእግሮቹ፡መካከል፥ገዢ፡የኾነው፡እስኪ መጣ፡ድረስ፤የአሕዛብ፡መታዘዝም፡ለርሱ፡ይኾናል"

ባጠቃላይ መጻፍ ቅዱስ የሚባለው ብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳን እንደሆነ ሁሉ ፣

ቅዱስ ፓትርያርኩ የብሉይ ኪዳን እና የአዲስ ኪዳን ምሳሌ የህነውን፣
👉 በግራ እጀቸው ጥንታዊቷን ያረጀችውን (ብሉይ)ን "በትረ ሙሴን ተመርኩዘው ፣
👉 በቀኝ እጃቸው የተሰቀለውን የእየሱስ ክርስቶስ መስቀል ይዘው፣
መከራ ቢመጣ መከራን ታግሰው እረኝነታቸውን በንቃት እንደሚወጡ ያሳያል።

የአዲስ ኪዳኑ እረኞች ጠባቂነታቸውን ከጌታችን ከመዳኒታችን ከእየሱስ ክርስቶስ ተቀብለዋል"... ግልገሎችን አሰማራ ጠቦቶቼንም ጠብቅ.. በጎቼንም አሰማራ" ባላቸው መሰረት ከሌሎች ብጹዓን ጳጳሳት ለየት ብለው ለጠባቂነታቸው ምልክት በግራ እጃቸው" በትረ ሙሴን " በቀኝ እጃቸው የወርቅ መስቀል ጨብጠው ይታያሉ።

ፓትርያሪኩም ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው “በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ” ተብለው አደራ የተቀበሉ ስለሆነ፣ የመሪነታቸው ምልክት ይህን በትር ይይዛሉ።

በትሩ ይመለክበታል⁉

የአባትነታቸው የመሪነታቸው ምልክት እንጂ በትሩ አይመለክም። ቢመለክ ሰባብረን እንጥለዋለን፣ የሚስመውም ሆነ የሚሰግድለት ማንም የለም፣ በትሩ ለመሪነታቸው ብቻ ምልክት ነው የማያገለግለው።

ወስብኀሃት ለእግዚአብሔር

Loading comments...